Qerro Media Service - QMS's Post

የፌዴራሊስት ሃይሎች ጥምረት ያወጣው አስራ አንድ ዋና ዋና ነጥቦች

1.የፌዴራሉ መንግስት በንፁሃን ዜጎች ላይ የሚያካሂደውን ግድያና የግፍ ተግባር በአስቸኳይ በማቆም ለሰላማዊ ሽግግር ዝግጁነቱን እንዲገልፅ፤

2.በፌዴራልና በክልሎች በፖለቲካ አመለካከታቸው ምክንያት የታሰሩ ዜጎችን በሙሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች መሪዎችን ጨምሮ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ከእስር እንዲፈታ፤

3.ሁሉም የሌሎች አገሮች የፀጥታ ሃይሎች በተለይም የኢሳያስ መንግስት ያሰማራቸው የፀጥታ ሃይሎች ከአገራችን በአስቸኳይ እንዲወጡ እንዲደረግ፤

4.በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ላይ የተጫነው ወታደራዊ አስተዳደር እንዲነሳ፤ ኮማንድ ፖስቶች እንዲፈርሱ፤ የፌዴራሉ መከላከያ ሰራዊት በህገመንግስቱ በተሰጠው ተልዕኮ እንዲገደብ፤ ክልሎች በህገመንግስቱ የተሰጣቸውን ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር መብታቸውን እንዳይጠቀሙ የሚሰነዘርባቸው ጥቃት እንዲቆምና በፌዴራልና በክልል ደረጃ ሰላምን የማስጠበቅና ህግ የማስከበር ስራ በብቸኝነት ለፌዴራልና ለክልል ፖሊስ ሃይሎች እንዲተው፤

5.ሁሉም ኢትዮጵያዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የኢትዮዽያ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ተወካዮች የሚሳተፉበትና ሰፊ ህዝባዊ መሰረት ያላቸው የፌዴራልና የክልል የብዙሃን ማህበራትና የሙያ ድርጅቶችን ያካተተ ሃገራዊ የመድህን ሸንጎ እንዲመሰረት፤ ሸንጎው በአገሪቱ ለተከሰተው ቀውስ ምክንያት የሆኑ ፖለቲካዊ ችግሮችን መፍታት የሚቻልባቸውን ስትራቴጂዎችንና መፍትሄዎችን እንዲመክር፤ እንዲሁም በአገሪቱ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ተካሂዶ በህዝብ ተቀባይነት ያለው መንግስት የሚመሰረትበትን ሁኔታ እንዲያመቻች፤

6.የሸንጎ ምስረታውን ሂደት የሚያስተባብሩ በህዝብ ዘንድ አመኔታ ያተረፉና በሁሉም ወገን ተቀባይነት ያላቸው እና የኢትዮዽያ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ስብጥር ግምት ውስጥ ያስገባ የአገር ሽማግሌዎች ቡድን እንዲቋቋምና የሰላምና የአገር መድኅን ሸንጎ ምስረታውን እውን እንዲያደርጉ፤

7.ሸንጎው በአገሪቱ ያሉትን ችግሮች ተወያይቶ ለሃገሪቱ ፖለቲካዊና ህገመንግስታዊ ችግሮች የጋራ መፍትሄ እስከሚያስቀምጥ፤ ህገ መንግስታዊ ስርዓቱ በሚፈቅደው መሰረትና በፖለቲካ ሂደቱ ያገባኛል ባይ አካላት ጋር በሚደረግ ምክክር አገሪቱን የሚያስተዳድር የኢትዮዽያ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ስብጥር ግምት ውስጥ ያስገባ የባለሙያዎች የባላደራ መንግስት እንዲመሰረት፤

8.በኢህአዴግ ዘመን ተፈፀሙ የሚባሉትንና በተመሳሳይ መልኩ ከመጋቢት 2010 ዓ.ም. ወዲህ የተፈፀሙ የሰብአዊ መብት ጥሰት ተግባራት፤ ጅምላ ጭፍጨፋዎችን፣ የፖለቲካ ግድያዎችን፣ ዘረፋና የውንብድና ተግባራት የሚያጣራ ገለልተኛ ቡድን እንዲመሰረትና ውጤቱን ለህዝብ ይፋ እንዲያደርግ፤ በይቅርታ የማይታለፉና በህግ ፊት ቀርበው መታየት ያለባቸውን ጉዳዮች ለይቶ እንዲያቀርብ፤

9.የሚድያ ተቋማት በህገ-መንግስት የተሰጣቸውን ተልዕኮ ብቻ በመወጣት አገርን በማዳን ተግባር ላይ እንዲያተኩሩ እንዲደረግ፤ ለዚህም ተግባራዊነት በጋራ ስምምነት ላይ የሚደረስበት አሰራር ተግባራዊ እንዲሆን፤

10.አህጉራዊና አለማቀፍ የሰላምና የደህንነት ስጋትን ማስወገድ ይቻል ዘንድ ኢትዮጵያን ከጥፋት ለማዳን በሚደረገው ጥረት አህጉራዊና አለማቀፍ አጋሮች ድጋፍ እንዲያደርጉ፤

11. ይህንን ታሪካዊ አገርን የማዳን ተግባር በመደገፍ መላ የአገራችን ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች፤ የኢፌዴሪ የመከላከያ ሰራዊት አባላትና ሁሉም የፖለቲካ ሃይሎችና የሲቪክ ድርጅቶች ሃገራዊ የመድህን ጥሪውን በመደገፍ እንዲሰለፉ የሰላም ጥሪ እናቀርባለን፡፡

የኢትዮዽያ ፌዴራሊስት ኃይሎች ጥምረት ለአገራዊ መድህን
መስከረም 2013 ዓ.ም
አዲስ አበባ
ኢትዮጵያ
By: via Qerro Media Service - QMS

No comments:

Post a Comment

Featured post

Ethiopia’s controversial quest for the sea

https://ift.tt/4t29xJd Ethiopia is famously landlocked. That’s why the ambitious Ethiopian prime minister Abiy Ahmed has long harbored visi...