Qerro Media Service - QMS's Post

ሀገራችን ውስጥ ለተከሰተው ወቅታዊ የፖለቲካዊ ችግር ፖለቲካዊ መፍትኼ ያሻል፡፡
ከኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ) የተሰጠ መግለጫ

=================|================
ብዙ የሰው ሕይወትና ንብረትን የጠየቀው፤ በተለይም በሺህ የሚቆጠሩ የቄሮዎች ሕይወት ተገብሮበት የመጣውና ተስፋ ሰጭ የተባለው ለውጥ አጣብቂኝ ውስጥ ከገባ ውሎ አድሯል፡፡ ዓይናችን እያየ ሞት፣ እስር፣ መሰደድ፣ መደብደብ ተመላልሶ መጥቶብናል፡፡ ለውጡም አደገኛ መስቀለኛ መንገድ ይገኛል፡፡

ፓርቲያችን ኦፌኮ፤ ለውጡ የተሻለ መንገድ እንዲይዝ ላለፉት ሁለት ዓመታት ውይይቶችንና ምክክሮችን በተለያዩ ደረጃዎች አድርገናል፡፡ ችግሮች ሲፈጠሩ ነገሮች ይስተካከሉ ዘንድ መግለጫዎች ጭምር አወጥተናል፡፡ አመራሮቻችንም ከተለያዩ የሀገር ውስጥ ሚዲያዎች ጋር ብዛት ያላቸውን ቃለ ምልልሶች አድርገናል፡፡ የገዥው ፓርቲ አካል ከሆነው የኦሮሚያ ክልል ክንፍ ጋር አብሮ መስራት እንዲቻል እና እስርና እንግልት ከሕዝባችን ላይ ይቆም ዘንድ ሰፊ ውይይቶችን አድርገናል፡፡ ጥረታችን ግን የተፈለገውን ውጤት አላመጣም፡፡ ነገሮች ተመልሰው እየተበላሹ ከመሄዳቸው የተነሳ የመንቀሳቀስ ዕድል እንኳን እየጠበበ በየዞኑና ወረዳዎች የተከፈቱ የኦፌኮ ጽ/ቤቶች ሲዘጉ ነበር፡፡ ችግሮች እየሰፉ ሲመጡ የእርምት እርመጃዎች እንዲወሰዱ ጉዳዩ የሚመለከታቸውን የመንግስት ባለሥልጣናትን አነጋግረናል፡፡ ደብዳቤዎችና አቤቱታዎችን አቅርበናል፡፡ ለምሳሌ፡-

በደብዳቤ ቁጥር ኦፌኮ/764/12 በቀን 14/06/2012 የኢፌዲሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአወዳይ ከተማ ማህበረሰብ ላይ የተፈጸመው የጭካኔ ዕርምጃ እንዲጣራና ውሳኔ እንዲሰጥ ጠይቀናል፡፡
በቁጥር ኦፌኮ/792/12 በቀን 21/08/2012 በየቦታው የታሰሩ አባሎቻችንና ደጋፊዎቻችን እንዲፈቱ እና መንግስታቸው የእርምት እርምጃ እንዲወስድ ለተከበሩ ዶ/ር አቢይ አህመድ የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትርን በደብዳቤ ጠይቀናል፡፡

ሁኔታዎች እየተባባሱ ሲሄዱ ለኢፌዲሪ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን በቁጥር ኦፌኮ/797/12 በቀን 02/10/2012 በመንግስት ኃይሎች በዜጎች ላይ የሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶች እንድጣራና ዕርምጃ እንዲወስዱ በማለት አቤቱታ በአድራሻ አቅርበን በግልባጭ ደግሞ ለኢፌዲሪ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ እና ለኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ አሳውቀናል፡፡ በአካልም ቀርበን የጉዳዩን አሳሳቢነት ገልጸናል፡፡

ከሁሉም በላይ ኦፌኮ አባል የሆነበት የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ከምርጫ 2012 መተላለፍ ጋር ተያይዞ ሊያጋጥም የሚችለውን ሕገ መንግስታዊ እና ፖለቲካዊ ቀውስ በተሻለ ለመውጣት ይቻላል ብለን ያሰብነውን አማራጭ የመፍትኼ ሐሳብ ግንቦት 4 ቀን 2012 ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አቅርበናል፡፡
ከአርቲስት ሃጫላ ሁንዴሳ መገደል በኋላ ደግሞ ሁኔታዎች የበለጠ እየተወሳሰቡ መጥተዋል፡፡ በተለይ ፓርቲያችን ሊመጣ የሚችለውን ውስብስብ ሁኔታ በመገመት የአርቲስቱ ግድያ በነፃና ገለልተኛ አካል እንዲጣራና ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ፤ እንዲሁም ግድያውን ተከትሎ የመጣው እስራትም እንደማይጠቅምና ይልቁንም የታሰሩት አባሎቻችን ተፈትተው ሀገርን የማረጋጋቱ ሥራ ላይ እንዲሳተፉ ቢደረግ የተሻለ ምርጫ መሆኑን በመገለፅ ጠይቀናል፡፡ አዎንታዊ መልስ እየጠበቅን እያለ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ ታይቶ በማይታወቅበት ሁኔታ መደበኛ ማቆያዎች በመሙላታቸው የትምህርት ቤት መማሪያ ክፍሎች ለኮሮና ቫይረስ በሽታ በሚያጋልጥ ሁኔታ እስር ቤቶች ሆነዋል፡፡ ካለን የግንኙነት መስመሮች ለመረዳት የቻልነው የወጣቱ ጥያቄም ከየሃጫሉ ገዳዮች ለሕግ ይቅረቡ መልስ ወደ የፖለቲካ እስረኞች ይፈቱ ሊዞር እንደሚችልም አሳውቀናል፡፡

እንደፈራነውም አልቀረ ብዛት ባላቸው የኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አከባቢዎች ሁኔታዎች ከፍጥጫ አልፈው በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ ታስረዋል፡፡ ደጋግመን እንዳሳወቅነው የሀገራችን ችግሮች በአብዛኛው የፖለቲካ ችግሮች ናቸው፡፡ መፍትኼውም ፖለቲካ መሆን አለበት፡፡ ከዓለምም ሆነ ከራሳችን ተሞክሮ እንደምንረዳው የፖለቲካ ችግር በዋናነት የሚፈታው በእስርና ጠመንጃ ሳይሆን በራሱ በፖለቲካ ነው፡፡

ስለሆነም፤ የኢፌዲሪ መንግስት የኃይል እርምጃዎቹን በአስቸኳይ አቁሞ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትን ከእስር በመፍታት ሀገሪቷ እንዲትረጋጋ እንዲያደርግና ሀገሪቷንና ሕዝቦቿን ወደ ብሔራዊ መግባባት እንዲመራ በአፅንኦት እንመክራለን፡፡

የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ
ፊንፊኔ፤ ነሐሴ 16/2012
By: via Qerro Media Service - QMS

No comments:

Post a Comment

Featured post

Ethiopia’s controversial quest for the sea

https://ift.tt/4t29xJd Ethiopia is famously landlocked. That’s why the ambitious Ethiopian prime minister Abiy Ahmed has long harbored visi...